የኢትዮጵያ ኢንቨስትመትን ሆልዲንግስ (ኢኢሆ) የ2017 በጀት ዓመት አፈጻጸም ውጤትና ቀጣይ አቅጣጫዎች
ሀገራችን ኢትዮጵያ በርካታ የኢኮኖሚ ልማት ሊያስገኙ የሚችሉ ተጨባጭ አቅሞች አሏት። ከእነዚህም ውስጥ ከ130 ዓመታት በላይ ያስቆጠሩትን ጨምሮ በርካታ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች፣ የመሬት ይዞታዎች፣ ብሎም ሌሎች ቁሳዊ ያልሆኑ ሀብቶችን አላት። የተለያዩ የልማት መሳሪያዎችን በመጠቀም፤ አዲስ የሀብት ምንጭ እና አቅም በመፍጠር፤ የተበታተነን የመንግስት ሃብት በማሰባሰብ እና የተሻለ የአመራር ብቃትን በመፍጠር እሴትን ማሳደግ እንዲሁም ሙሉ በሙሉ ሀብቶችን በውጤታማነት በማስተዳደር ጥቅም ላይ ማዋልና ዋጋቸውን ከፍ በማድረግ ያለን አቅም አሟጦ መጠቀም አስፈላጊ ነው፡፡ ስለሆነም እነዚህን ዓላማዎች ከግብ ለማድረስ እና የተለያዩ የመንግሥት ሃብቶችን ለማሰባሰብ፣ ለማስተዳደር፣ ለማብዛት እንዲሁም ተጨማሪ ሀብት ወደ ሃገራችን እንዲፈስ ለማድረግ፣ በመንግሥት ሙሉ ባለቤትነት የተያዘ የልማት ድርጅቶችን በአንድ ማዕቀፍ በባለቤትነት ማስተዳደርን ታሳቢ ተደርጎ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመትን ሆልዲንግስ በአዋጅ ቁጥር 1263/2014 እና ዝርዝር ስልጣንና ተግባሩን ለመወሰን በወጣው የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 487/2014 ተቋቁሟል፡፡
የኢትዮጵያ ኢንቨስትመትን ሆልዲንግስ (ኢኢሆ) በህግ ከተሰጠው ስልጣንና ሃላፊነት ውስጥ ዋናው ሆልዲንጉ በባለቤትነት የሚያስተዳድራቸው የመንግስት የልማት ድርጅቶችን አለማቀፍ ተወዳዳሪ ተቋማት እንዲሆኑ በዘመናዊ የኮርፖሬት አስተዳደርና ፋይናንስ ስርዓት መመራታቸዉን ማረጋገጥ ነው፡፡ ይህንን ሃላፊነቱን ለመወጣት በርካታ ተግባራትን የሚያከናውን ሲሆን ከነዚህ ተግባራት መካከል የድርጅቶችን አፈጻጸም በየወቅቱ በመፈተሽ ያሉበትን ደረጃ በመገምገም የማሻሻያ አቅጣጫዎችን ያስቀምጣል፡፡
በዚህም መሰረተ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመትን ሆልዲንግስ በባለቤትነት የሚያስተዳደራቸውን የመንግስት የልማት ድርጅቶችን የ2017 በጀት ዓመት አፈጻጸም እና የ2018 ዕቅዶችን ከእያንዳንዱ የልማት ድርጅቶች የቦርድ ተወካዮችና አመራሮች ጋር ጠለቅ ያለ ውይይት በማድረግ ገምግሞ አጽድቋል። የእያንዳንዱ ድርጅት አፈጻጸም ግምገማ እንደ ተቋሙ የኢንዱስትሪ ባህርይ፣ ያለበት የአፈጻጸም ደረጃ ከሀገራዊ ፍላጎት እና እድገት፣ ቀጠናዊ እና አለም አቀፋዊ ተወዳዳሪነት አኳያ የተለያዩ እይታዎችን የተከተለ ሲሆን ዋና ዋናዎቹም ኦፕሬሽን (ወይም የምርትና አገልግሎት እድገት፣ የጥራትና የአቅም አጠቃቀም)፣ ፋይናንስ (የገቢ እድገት፣ ትርፋማነት፣ የሃብት አጠቃቀምና የፋይናንስ ጤናማነት)፣ የኮርፖሬት አስተዳደር (የዳይሬክተሮች ቦርድ ተሳትፎና ስትራቴጂክ ድጋፍ፣ የውስጥ ኦዲት ቁጥጥር፣ የፋይናንስ ሪፖርት ወቅታዊነት እና የስጋት አስተዳደር)፣ ብቁ አመራር (ስትራቴጂ፣ የሰው ሃይል፣ የፕሮጀክት አፈፃፀም፣ ዘመናዊ አሰራር እና ዲጂታይዜሽን፣ የምርት ስርጭት/አገልግሎት ተደራሽነት እና ደንበኛ አያያዝ)፣ እንዲሁም የአካባቢና ማህበራዊ ግዴታዎች መወጫ ትግበራዎችን ያማከሉ ናቸው።
ባጠናቀቅነው የ2017 ዓ.ም. በጀት አመት በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ስር የሚገኙ ተቀጥላ ድርጅቶች በበጀት ዓመቱ አጠቃላይ ገቢያቸው 2.05 ትሪሊዮን ብር ያገኙ ሲሆን የአጠቃላይ የኢኢሆ ፖርትፎሊዮ አማካይ የተጣራ ትርፍ ከታክስ በፊት ከ262.7 ቢሊዮን ሲሆን ይህም በቅደም ተከተል ከባለፈው አመት ተመሳሳይ ወቅት በ88% እድገት አሳይቷል። በተለይም ለሃገሪቱ ኢኮኖሚ ምስሶ የሆኑት ትላልቅ ኩባንያዎች ከባለፈው የበጀት ዓመት ከፍ ያለ ምርት እና አገልግሎት ለህዝብና ለዓለም አቀፍ ማህበረሰብ አቅርበዋል።
በዚህም መሰረት
ኢትዮ ቴሌኮም የድምጽ ጥሪ አገልግሎት የደንበኞች በ7 በመቶ እንዲሁም የኢንተርኔት አገልግሎት ደምበኞች በ15 በመቶ ጨምሯል
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተቀማጭ በ310 በመቶ እንዲሁም ለግል ዘርፍ ደንበኞች ያቀረበው ብድር በ104 በመቶ ጨምሯል
የኢትዮጵያ አየር መንገድ አገልግሎት የሰጣቸው ተጓዦች ቁጥር በ11 በመቶ ጨምሯል
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የደንበኞች አጠቃላይ ለፍጆታ የቀረበ የሃይል መጠን በጊጋዋት ሰዓታት በ18.2 በመቶ ጨምሯል
የኢትዮጵያ ግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የማዳበሪያ ስርጭት መጠን በ18 በመቶ ጨምሯል
የወንጂ ስኳር ፋብሪካ ያመረተው የስኳር ምርት መጠን በ113 በመቶ ጨምሯል
ከኢንዱስትሪ አንጻር የተገኘው የትርፍ ከታክስ በፊት ድርሻ ስንመለከት
የፋይናንስ አገልግሎት 14.95%
ትራንስፖርትና ሎጂስቲክ 66.8%
ሃይልና ግንኙነት 10.08%
ንግድ 2.02%
ግብርናና አግሮ ፕሮሰሲንግ 2.64% ደርሷል።
የኢኢሆ ተቀጥላ ድርጅቶች ማክሮ ሪፎርሙ ያመጣቸውን እድሎች አሟጦ በመጠቀም እና ፈተናዎችን በመቅረፍ ላሳዩዋቸው ጠንካራ አፈጻጸሞችን በማመስገንና ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ተጨማሪ ግብዓቶችን በመስጠት፤ እንዲሁም መሻሻል የሚገባቸው ጉዳዮች ላይ ግልጽ ውይይት ከተደረገ በኋላ በቀጣይ ሊስተካከሉ የሚገባቸው ጉዳዮች ላይ አቅጣጫ በማስቀመጥ እንዲሁም በ2018 በጀት ዓመት እና በቀጣይ ስትራቴጂክ ዘመን በትኩረት ሊታዩ የሚገባቸው ጉዳዮች ላይ ስምምነት ደርሷል። ይህን ስመልክቶ ከተነሱ አንኳር አቅጣጫዎችና የቤት ሥራዎች መካከል፦
- የደንበኞችን እርካታ ለማረጋገጥ፣ ሀገራዊ ፍላጎትን እና እድገትን የሚመጥን እና የገበያ ፉክክርን በአሸናፊነት ለመወጣት የምርትና የአገልግሎት ጥራት ማሻሻል፣
- እጅ ላይ ያሉ ሃብቶችን አሟጥጦ መጠቀም እንዲሁም የአመራረት ስልቶችና እና አገልግሎት አሰጣጦች ቴክኖሎጂዎች ተግባራዊ በማድረግ ወደ ዘመናዊ አሰራር ለመሸጋገር የተለያዩ የፋይናንስ ምንጮችን ማፈላለግ፣
- ዘላቂ እድገት ለማስገኘት ኢንቨስትመንት አፈጻጸምን ከፋይናንስ ጤናማነት ጋር አጣጥሞ ማስኬድ፣
- የፋይናንስ መረጃ አያያዝን አስተማማኝ ለማድረግ የሰው ሃይልና የቴክኖሎጂ አቅምን መገንባት፣
- ለተቋማዊ ስኬት መሠረት የሆነውን የሰው ሃይል እቅም፣ የሥራ ቦታ ምቹነትና የደሞዝና ሌሎች ጥቅማ ጥቅሞች ተገቢነት በቅርብ መከታተል፤ አትጊ የሆነና ለተጠያቂነት የሚያመች ዘመናዊ የምዘና ሥርዓት መዘርጋት፣
- በተለያዩ ዘርፎች ላይ የሚታዩ የፖሊሲና አፈጻጸም ክፍተቶችን ለመዝጋት ከኢኢሆና ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር ውይይትና ትብብር ማድረግ፣
የሚሉት ዋና ዋናዎቹ ናቸው።
ሁሉም ድርጅቶች በኢኢሆ በኩል የተሰጡ ግብረ መልሶችና ቀጣይ አቅጣጫዎች በዓመታዊና የረጅም ጊዜ እቅዶች ለማካተትና ለመተግበር ኢኢሆም የሚጠበቅበትን ድጋፍ ለማድረግ ስምምነት ላይ ተደርሷል። ከዚህም በተጨማሪ በ2018 ዓ.ም. የልማት ድርጅቶች አጠቃላይ ገቢ 2.75 ትሪሊዮን ብር እና 412 ቢሊዮን ብር ትርፍ ከታክስ በፊት ለማድረስ ታቅዷል።
የኢትዮጵያ ኢንቨስትመትን ሆልዲንግስ ለበጀት ዓመቱም ሆነ ለአፈጻጸም ግምገማ ሂደቱ መሳካት ሚናቸውን ለተጫወቱትን የኩባንያ የዳይሬክተሮች ቦርዶች፣ የየድርጅቶቹ አመራርና ሠራተኞች ብሎም ለባለድርሻ አካላት ምስጋና ያቀርባል።
ነሐሴ 2017 ዓም
አዲስ አበባ
Post Views: 809